ንግድ ምክር ቤቶቹ ወዴት?
የንግድ ምክር ቤቶች ምሥረታ ታሪክ የሚጀምረው ከአዲስ አበባ ነው፡፡ በ1947 ዓ.ም. አካባቢ በአዲስ አበባ የነበሩ የውጭና የአገር ውስጥ ነጋዴዎች የአዲስ አበባ ነጋዴዎች ማኅበር በሚል ስያሜ የጀመሩት እንቅስቀሴ የንግድ ምክር ቤቶች ምሥረታ ፈር ቀዳጅ ነው፡፡
በወቅቱ በንግድ ሥራ በተለይ በዘመናዊ በሚባል የንግድ አሠራር ይንቀሳቀሱ የነበሩት የውጭ ኩባንያዎች ስለነበሩ ከማኅበርተኞችም ብልጫ ይይዙ የነበሩት እኚሁ የውጭ ኩባንያዎች ናቸው፡፡ የማኅበሩ የመጀመርያ ፕሬዚዳንትም በመሆን የተሰየሙት የውጭ ዜግነት ያላቸው ግለሰብ እንደነበሩ ይነገራል፡፡
ከዚህ በኋላ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የንግድ ምክር ቤት አስፈላጊነቱን በማመን ለማኅበሩ እውቅና በመስጠት የራሱ የሆነ ሕንፃ እንዲኖረው አድርገዋል፡፡ የኢትዮጵያና የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤቶች አመሠራረትም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው፡፡
ምክር ቤቶቹ በተለያዩ አደረጃጀት 69 ዓመታት ዘልቀዋል፡፡ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መልካም ፈቃድ ታክሎበት ዛሬ ሜክሲኮ አደባባይ የሚገኘውን ባለ ሰባት ፎቅ ሕንፃ ለመገንባት ተችሏል፡፡
በወቅቱ 1.8 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት ሕንፃ ከተገነባ በኋላ የአዲስ አበባም ሆነ የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤቶች የራሴ የሚሉት ተጨማሪ ሕንፃ መገንባት ሳይችሉ 70 ዓመታት ሊደፍኑ ነው፡፡
ከ65 ዓመታት በፊት የተገነባው ሕንፃ በደርግ ተወርሶ ድጋሜ ለንግድ ማኅበረሰብ የተመለሰው በ1999 ዓ.ም. ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ሕንፃው የባለቤትነት ጉዳይ የአዲስ አበባና የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤቶች ሲያወዛግብ እንደነበር ይታወሳል፡፡
የመንግሥት እገዛ ቢኖረውም ጥቂት አባላትን ይዞ ከ65 ዓመታት በፊት የነበረው የንግድ ኅብረተሰብ ሕንፃ ለመገንባት ችሏል፡፡ አሁን ደግሞ በሺዎች የሚቆጠሩ አባላትን የያዘው የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤትም ሆነ በአገሪቱ ውስጥ ያሉ ሌሎች ንግድ ምክር ቤቶች በተናጥልም ሆነ በጋራ የራሴ የሚሉት ሕንፃ ለመገንባት ሐሳብ ማፍለቅ ከጀመሩ ገና አንድ ዓመት እንኳን አልሞላውም፡፡
በንጉሡ ዘመን የንግድ ምክር ቤት አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ እንደ ቀድሞው የአዲስ አበባና የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ክቡር ገና ገለጻ፣ በአፄው ዘመን የነበሩ የንግድ ምክር ቤት መሪዎች የተመረጡት በራሳቸው የሥራ ደረጃና በሥራቸው ያገኙት ውጤት ተመዝኖ ነበር፡፡ ምርጫ የሚባልም ነገር አልነበረም፡፡ የሚተዋወቁ ይጠራሩና የተሻለው እንዲመራ ይደረጋል፡፡
በደርግ ዘመነ መንግሥት ደግሞ ቀደም ብሎ የነበረው አሠራር ተቀይሮ እያንዳንዱ ነጋዴ የምክር ቤቶቹ አባል የሚሆነው በግዳጅ ሆነ፡፡ የንግድ ፈቃድ የሚያወጣ ነጋዴ ፈቃዱን በእጁ ያስገባ ዕለት የንግድ ምክር ቤቱ አባል ይሆናል፡፡ ለአባልነት የተጣለበትን ዓመታዊ መዋጮ ይከፍላል፡፡
አባልነቱ በፍላጐት ላይ የተመሠረተ ባለመሆኑ የአባላቱ ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም፣ የንግድ ምክር ቤቶቹ እንቅስቃሴ ከአንድ መንግሥታዊ ተቋም ብዙም ባልተለየ የሚጓዝና፤ አባላቶችንም ለመደገፍ የሚደረግ ሥራ አልነበረም፡፡ ‹‹ምርጫ ስለመኖሩም እጠራጠራለሁ›› የሚሉት አቶ ክቡር፣ ፍላጐት በመቅረቱ የግል ዘርፍ አለ ብዬ ለመናገር ስለማልችል በደርግ ዘመን የንግድ ምክር ቤት በስም የነበረ ብቻ ነው ይላሉ፡፡
አገሪቱ ትከተል የነበረው የሶሻሊስት ሥርዓት በመሆኑ፣ የንግድ ምክር ቤቶች ዓላማና ግብ ከሥርዓቱ ጋር የተሳሰረ ነበር፡፡ ትክክለኛውን የንግድ ምክር ቤቶች ክንዋኔዎች ያልተገበሩበት ወቅት እንደነበር ተደርጐ ይወሰዳል፡፡
ከደርግ ውድቀት በኋላ ግን የነፃ ኢኮኖሚና ገበያ ሥርዓት በመታወጁ የንግድ ምክር ቤቶች በተወሰነ ደረጃ ዓይናቸው ተገልጧል፡፡ በቀድሞ ሥርዓት አባልነት በግዴታ ይሆን የሚለው ድንጋጌ ተሽሮ አባልነት በፈቃደኝነት ላይ መመሥረት አለበት ወደሚለው አሠራር ተገባ፡፡ የአገሪቱ የንግድ ምክር ቤቶች እንቅስቃሴ ሲወሳ ቀድሞም ሆነ አሁን በግንባር ቀደምትነት የሚቀጠሰው የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ስለነበር ከደርግ ውድቀት በኋላም የተሻለ የሚባል ነበር፡፡ በተለይ ከ1988 ዓ.ም. አካባቢ ጀምሮ አዳዲስ ነገሮች መታየት ጀመሩ፡፡
ንግድ ምክር ቤቱን የሚመሩ አዳዲስ አመራሮች ብቅ አሉ፡፡ በንግድ ምክር ቤቱ ታሪክ ዘመናዊ የሆነ የንግድ ምክር ቤቶች እንቅስቀሴ የታየው ወይም ከዓመታት በኋላ ንግድ ምክር ቤቶች እንደ አንድ ወሳኝ ተቋም መታየት የቻሉት በ1988 ዓ.ም. አካባቢ ነው፡፡
ምክር ቤቱን ወደ ላቀ ደረጃ እናሸጋግራለን ብለው በፈቃደኝነት ጭምር ወደ አመራር ከመጡት ግለሰቦች መካከል አቶ ክቡር ገናና አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ ይጠቀሳሉ፡፡ በቦርድ አባልነት ለማገልገልም እንዲሁ ከጊዜው ጋር ሊራመዱ የሚችሉ የንግድ ኅብረተሰቡ አባላት በቦርድ ውስጥ ተካትተዋል፡፡
በወቅቱ ለንግድ ምክር ቤቱ እንግዳ ሆኖ የነበረው አዳዲሶቹ የምክር ቤቱ አባላት ወደ አመራር ለመውጣት የፈጠሩት አዲስ የምርጫ አካሄድ ነበር፡፡ ምክር ቤቱን እናገለግላለን በማለት የቀረቡት እነዚህ ግለሰቦች፣ ከዚህ ቀደም ከተለመደው አሠራር ውጭ በፕሬዚዳንትነት ለመመረጥ እንዲህ አደርጋለሁ፣ እንዲህ እሠራለሁ ብለው በመቀስቀስ ወደ ምርጫ ገቡ፡፡ ነጋዴዎች ይገኙበታል ወዳሉት መርካቶ ድረስ በመዝለቅ መቀስቀሳቸው ብዥታ እስከመፍጠር ደርሶ ነበር፡፡
በዚህ ስልት ተወዳድረው አቶ ክቡር አሸንፈው የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሆኑ፡፡ በምክር ቤቱ የዓመታት የሥራ ሒደት አዳዲስ የሚባሉ አሠራሮች ተዘረጉ፡፡ የጽሕፈት ቤቱም አደረጃጀት ተለወጠ፡፡ ‹‹ይቻላል›› የሚለው የምክር ቤቱ መለያም በዚህ ወቅት ነበር ብቅ ያለው፡፡
‹‹ይቻላል›› የሚለው መሪ ቃል እስከዛሬ ድረስ የምክር ቤቱ መለያም ሆኖ ከንግድ ምክር ቤቱ አርማ ጐን ሳይለይ ዘልቋል፡፡ ይህ ቃል በወቅቱ የነበረው ቢሮክራሲ መስፋፋት ጋር የተያዘ የነበረውን ችግር ለመቅረፍ የራሱን እገዛ አድርጓል ተብሎ ይታመናል፡፡
አንድ ጉዳይ ለማስፈጸም የሚወስደውን ጊዜና አይቻልም የሚባሉ ጉዳዮች የሚቻሉ መሆናቸውን ለማሳየት ዕድል ሰጥቷል፡፡ በይቻላል መንፈስ የተጀመሩ ብዙ ጥረቶች ውጤት ማምጣታቸው፣ የመደማመጥ ባህል እንዲኖርና ግንዛቤ እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ በተለይ የቻምበር ፎረምና የምሳ ላይ ውይይቶች በዚሁ ጊዜ ተጀምሮ በተከታታይ ዓመታት ተጠናክሮ መቀጠል ችሏል፡፡ ዛሬም ድረስ የቻምበር ፎረም ይሠራበታል፡፡
ይህ የውይይት ፕሮግራም ቀደም ብሎ ያልተሞከረ መሆኑም የንግድ ምክር ቤቱ መነቃቃት የታየበት ወቅት ነው ሊባል ይችላል፡፡ ይህ የውይይት ፕሮግራም ነጋዴዎች በተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ግንዛቤ እንዲይዙ በባለሙያ የሚቀርብ ጽሑፍ ጭምር የሚያካትት በመሆኑ፣ በየወቅቱ ለውይይት የሚቀርቡ አጀንዳዎችን የመንግሥት አካላት እንዲያውቁት ስለሚደረግ ለፖሊሲ አውጭዎች ግብአት እንዲሆን ረድቷል የሚሉም አሉ፡፡ ይህም የንግድ ምክር ቤቶች አካሄድ ጠንካራ እየሆነ መምጣቱን ከማሳየቱ በላይ አባላት ወደ ንግድ ምክር ቤቱ እንዲቀርቡ አዲስ ዕድል ፈጥሯልም የሚል እምነት አሳድሯል፡፡
በተለይ በአገሪቱ ውስጥ የሚታወቁ ትላልቅ የሚባሉ ኩባንያዎች የንግድ ምክር ቤቱ አባል መሆን የቻሉበት ወቅም ተደርጐ ይወሰዳል፡፡ የኩባንያዎች ባለቤቶችም በቀጥታ የመሳተፍ ባህላቸው ጐልቶ መታየት የጀመረበት በመሆኑ በንግድ ምክር ቤቱ ታሪክ በተለይ የሚታይ ጊዜ ነው፡፡
ከአቶ ክቡር ገና በኋላም የተተኩት አቶ ብርሃነ መዋና ቦርዳቸው ቀደም ብሎ የተጀመረውን አሠራር አስቀጥለዋል ቢባልም፣ አካሄዳቸው የንግዱ ኅብረተሰብ አጀንዳ ውጭ እየተንቀሳቀሱ ነው መባሉ በንግድ ምክር ቤቱ ላይ የተለየ ድባብ እንዲፈጥር አድርጓል፡፡ ሆኖም በተለይ ለንግዱ ኅብረተሰብ ችግሮችን እንዲቃለሉ ከመንግሥት አካላት ጋር ውይይት እንዲካሄድ ግፊት በማድረግ በወቅቱ እንደችግር የሚነሱ ጉዳዮች ላይ ብዙ ሲሟገቱ ነበር፡፡ በመንግሥትና በንግድ ምክር ቤቱ መካከል የተጀመረው ውይይት ላይ የሚነሱ ጉዳዮች ግን በመልካም የታተዩ አይመስሉም ነበር፡፡
በአቶ ክቡር ገናና በአቶ ብርሃነ መዋ አመራር ወቅት ምክር ቤቱን በምክትል ፕሬዚዳንትነት ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉ ከአቶ ብርሃነ መዋ ከኃላፊነት ከለቀቁ በኋላ ፕሬዚዳንት ሆነው የቀድሞ አሠራር ቀጥሏል፡፡ አዳዲስ አሠራሮችም ተተግብረዋል፡፡ የአባላት ቁጥርም እያደገ መጥቷል፡፡ ይህ አካሄድ ምክር ቤቱ እየተለወጠ መምጣቱን ያሳያል፡፡ በአንፃሩ ከአዲስ አበባ ውጭ ያሉ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት እንቅስቃሴ የጐላ አልነበረም፡፡
ንግድ ምክር ቤቶች ከ1995 ዓ.ም. በኋላ
ከደርግ ውድቀት በኋላ መነቃቃት ታይቶባቸዋል የተባሉ ንግድ ምክር ቤቶች ያልተጠበቀ ውጥረት ውስጥ ገቡ፡፡ በተለይ የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት፣ የንግድ ምክር ቤቶችን እንደገና ለማቋቋም የሚወጣው አዋጅ አዲስ የቤት ሥራ ሆነባቸው፡፡ አደረጃጀታቸውን በአዲስ እንዲቀይሩ ያስገደደውን አዋጅ ተከትሎ እንደገና ለመደራጀት የወሰደው ጊዜ ንግድ ምክር ቤቶች በዚሁ አዋጅ መሠረት ለመደራጀት በሥራ ተጠመዱ፡፡ ሊሠሩ ይገባ የነበረውንም ሥራቸውን አቀዘቀዘው፡፡
የንግድ ምክር ቤቶች ከስያሜያቸው ጀምሮ እንዲለወጥ ተደረገ፡፡ ከንግዱ ጋር ዘርፎች እንዲቀላቀሉም ሆነ፡፡ ይህ አደረጃጃት መንግሥት ከሚፈልገው ፖሊሲ ጋር እንዲጣጣም ለማድረግ ቢሆንም፣ አዋጁ በአደረጃጀት ላይ ግን ክፍተት በመፍጠሩ ብዥታዎች ተከተሉ፡፡
በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ውስጥ በአገር አቀፍም ሆነ በክልል ደረጃ የተዋቀሩት የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች አንደኛው ችግር ከአዲሱ አዋጅ ጋር የተሳሰረ ስለመሆኑ ተደጋግሞ ይጠቀሳል፡፡ አዲሱ አዋጅ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህ በአገር አቀፍ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት በምክትል ፕሬዚዳንትነት ያገለገሉትና የትግራይ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉወርቅ ኪዳነማርያም እንደሚሉት፣ ‹‹ይህም አዋጁ የንግድ ምክር ቤቶች አደረጃጀትን በተመለከተ አተገባበሩ በተለይ በሰዎች የተለያየ አተረጓጐም እየሰጡት ብዥታ ይፈጥራል፡፡››
የንግድ ምክር ቤቶች ወቅታዊ ችግሮች አንዱም ይኸው አዲሱ አደረጃጀት የፈጠረው ነው የሚሉ አሉ፡፡ በአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባዔዎች ላይ ይገኙ የነበሩ የታላቅ ኩባንያዎች መመናመን አንዱ ምክንያት ተደርጐም ይወሰዳል፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ የንግድ ምክር ቤቶች አባላት እንደተጠበቀው ንቁ ተሳትፎ አለመኖር ደግሞ የንግድ ምክር ቤቶች ውስጣዊ ችግሮች በተለይ የእርስ በርስ ሽኩቻ ነው፡፡ ወደ አመራር ለመምጣት ውስጥ ለውጥ በሚደረግ ሽኩቻ ነጋዴዎች የንግድ ምክር ቤቶችን በጥንቃቄ እንዲመለከቱ አድርጓል፡፡ ቀድሞ የነበረ ድባብም እንዲደበዝዝ የራሱን አስተዋጽኦ ማድረጉን የሚናገሩም አሉ፡፡
የንግድ ምክር ቤቶች የእርስ በርስ ግንኙነት ያለመጠናከር፣ ኃላፊነቱን በአግባቡ አለመወጣትና በአመራር ደረጃ ያሉ ሰዎች ለራስ ስም መጨነቅ ሌሎች መገለጫዎች እንደሆኑም ይገለጻል፡፡ በየጊዜው የፈጠረው ችግርም በቀጠታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከቡድናዊ አሠራር ጋር ይያዛል፤ ይህም ንግድ ምክር ቤቶቹንም ጐድቷል፡፡
ባለፈው ሳምንት የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤትን በፕሬዚዳንትነት እንዲመሩ የተመረጡት አቶ ኤልያስ ነገቴ እንደሚሉት ደግሞ የመጀመርያ ሥራቸው አሉ የሚባሉ ችግሮችን ለመፍታት መጣር ነው፡፡ አንዱ ምክር ቤቱን ዓይን ውስጥ የከተቱ የፎረም አባላት ጉዳይን የሚመለከት መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ በተለይ ከኮረም መሙላት አለሙሙላት ጋር በተያያዙ የሚነሱ ችግሮችም ሆነ ሌሎችንም ችግሮች በቅድሚያ ካልተፈታ ለሥራ ስለሚያስቸግር፣ ይህንን የማስተካከል ሥራ ቅድሚያ እንደሚሰጠው ይናገራሉ፡፡
በየጊዜው ተፈጠሩ ለሚባሉ አለመግባባቶች ንግድ ምክር ቤቶች ሊሠሩ የሚገባቸውን ሥራ እንደመሥራት በቡድንተኝነት የሚሠራው ሥራ የንግድ ምክር ቤቶቹ አካሄድ ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ እያደረገ ነው፡፡ ወደ አመራር ለመምጣት የሚታየው ፉክክር ደግሞ ቅጥር ሠራተኞች ሳይቀሩ እጃቸውን ስለሚያስገቡበት ለንግድ ምክር ቤቶቹ ችግሮች መባባስ ምክንያት ሆኗል፡፡
የአባላት ወደ ንግድ ምክር ቤት ያለመምጣት ጉዳይም እንደ ችግር የሚታይ በመሆኑ፣ አባላት ወደ ንግዱ ምክር ቤት እንዳይመጡ የሆኑት ለምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄን በመያዝ ጥናት በማካሄድ መፍትሔ መስጠትም ቀዳሚ ሥራቸው እንደሚሆን የአቶ ኤልያስ ገለጻ ያስረዳል፡፡
ሌሎች የምክር ቤት አባላት ደግሞ ንግድ ምክር ቤቶች ለንግዱ ኅብረተሰብ የሚሰጡት አገልግሎት አርኪ ባለመሆኑ ምን ብሎ ወደ ምክር ቤት ይመጣል የሚል ትችት ይሰነዝራሉ፡፡ በተለይም በየጊዜው ተፈጠሩ የሚባለው ግጭት ለአባላት መሸሽ ምክንያት ነው በማለት ይገልጻሉ፡፡
እንደ አቶ ክቡር ገና ያሉት ደግሞ አሁን ባለው አካሄድ መሠረት የንግድ ምክር ቤቶች መኖር ምንም ጥቅም እንደሌለው ይናገራሉ፡፡ ሥራቸውን እየሠሩ ነው ማለት እንደማይቻልም ይጠቁማሉ፡፡ በተለይ አሁን የሚሰጡዋቸው አገልግሎቶች በግል ነጋዴ የሚሠሩ ስለሆነ የንግድ ኅብረተሰቡን ችግሮች በትክክል ያወቁ ንግድ ምክር ቤቶች አለመሆናቸውን ያክላሉ፡፡
አቶ ኤልያስ ደግሞ አባላትን ለማገልገል እየተሠራ መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ በተለይ በቅርብ ‹‹የኮል ሴንተር›› አገልግሎት ተግባራዊ ስለሚደረግ ነጋዴዎች ያለባቸውን ችግር በቀጥታ የሚገልጹበት ዕድል ስለሚኖራቸው ችግሮችን በቀላሉ ለመፍታት ይቻላል የሚል እምነት አላቸው፡፡
የንግድ ምክር ቤቶች እንቅስቃሴ ከቀድሞው ጋር ሲነጻጸር የተሻለ ነው እንደማይባልና ብዙ ችግሮች እንዳሉ የሚገልጹ አሉ፡፡ አቶ ኤልያስ ደግሞ ወቅታዊው ንግድ ምክር ቤት ከዚህ ቀደም በተሻለ የሚንቀሳቀስና የተንቀሳቀሰም መሆኑን በመግለጽ፣ የቀድሞ ይሻላል የሚለውን አይቀበሉም፡፡
እንደ አቶ ሙሉወርቅ ገለጻ ደግሞ የግለሰቦች ጣልቃ ግበነት መስተካከል መቻል አለበት፡፡ አቶ ሙሉወርቅ ጨምረው እንደገለጹት፣ የንግድ ምክር ቤቶች አደረጃጀትና የአዋጁ አተገባበር በተለይ ሰዎች የተለያየ ግንዛቤ እየሰጠ በንግድ ምክር ቤቶች መካከል ችግሮችን እየፈጠረ በመሆኑ ይህ መስተካከል አለበት ይላሉ፡፡
ሌላው በንግድ ምክር በቶች ውስጥ የሚመረጡ ሰዎች የአመራረጡ ሒደት ከጊዜ ወደ ጊዜ ችግሮቸ እየተስተዋሉበት በመሆኑ፣ የሕግ ማዕቀፎችን ማጠናር ሲገባ ይህ እየተሠራ ባለመሆኑ ክፍተት ተፈጥሯል፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ችግር ለመቅረፍ ደግሞ ብዙ መሠራት አለበት፡፡
በአዋጁ በተለይ አደራጁ አካል ሚናው ምንድነው? ለሚለው የተለየ ነገር የለም፡፡ ይህም ትልቅ ችግር ነው፡፡ የግለሰቦችም አመለካከት ሲገባ ደግሞ ክፈተቱን ያሰፉታል፡፡ ይህ አደረጃጀት ችግር መፈታት አለበት የሚሉት አቶ ሙሉወርቅ፣ ሁሉም ንግድ ምክር ቤቶች በራሳቸው ሥልጣንና ኃላፊነት አላቸው፡፡ በጋራም አንድ ኅብረት መሥርተዋል፡፡ ይህንን የጋራና የተናጠል ኃላፊነታቸው ምን ድረስ ነው? የሚለው ጉዳይም ተለይቶ መቀመጥ አለበት፡፡
‹‹ይህም ግለሰቦች በፈለጉት ወቅት የፈለጉትን ትርጉም እየሰጡ ነው፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ችግሮች የሚፈጠሩት በምርጫ ወቅት ነው፡፡ ስለሠሩት ሥራ ሳይታወቅ ምርጫ ወቅት ላይ ግርግር ይፈጥራሉ፡፡ ለነጋዴው ምን እንደሠሩ እንኳ አይታወቅም፡፡ አንዳንዴ እንደሚሰማው አንዳንዶች ቀጣሪያቸውን እስከማስቀጠር ደርሰዋል መባሉ አቅጣጫ እየተሳተ መሆን ያሳያልም፤›› ይላሉ፡፡
‹‹ስለዴሞክራሲና ስለመልካም አስተዳደር የሚጠይቅ አካል በራሱ ውስጥ መልካም አስተዳደር የማይታይበት ከሆነ ትልቅ ችግር ነው፡፡ በዚህ መልክ በምን ሞራል ከመንግሥት ጋር ሊደራደሩ ይችላሉ?›› በማለት የነገሩን አሳዛኝነት ይጠቅሳሉ፡፡ ስለዚህ ንግድ ምክር ቤቱን ከግል መገልገያነት ከማየት ይልቅ ለንግድ ኅብረተሰብ ቢሠሩ ይመረጣል ይላሉ፡፡
ከዚህ በኋላ ያሉ አመራሮችም ይህንን የንግድ ምክር ቤት ስም ሲያስነሱ የነበሩ ጉዳዮችን መቀየር እንዳለባቸውም ተጠቁሟል፡፡ ንግድ ምክር ቤት ይፍረስ እስከማለት የደረሱ አካላት ለምን እንዲህ እንዳሉ ሊፈተሽ ይገባል፡፡ ንግድ ምክር ቤቱ የንግድ ኅብረተሰቡን ያላገለገለ ሆኖ አግኝተውት ሊሆን እንደሚችል በማመን ለዚህ መሥራት ያስፈልጋል ባዮች ናቸው፡፡ በተለይ አላሠራ እያለ ነው ያለውን አዋጅ እንዲስተካከል ማድረግ የብዙዎች እምነት ነው፡፡