ከዚህ ቀደም የአገልግሎቶች አሰጣጥ ሲሳከርና ሲቋረጥ ከመንግሥት ማብራሪያና ይቅርታ እንደሚጠበቅ ማሳሰባችን አይዘነጋም፡፡
አሁን ደግሞ ማብራሪያና ይቅርታው ሲጠፋ መደበቅን ምን አመጣው ለማለት እየተገደድን ነው፡፡ በተለይ በመንግሥት ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ እየታየ ያለው እጅግ በጣም አጠያያቂ ጉዳይ የዛሬው መነጋገሪያችን ነው፡፡

በእርግጥ በማንኛውም ሥራ ውስጥ ችግሮች እንደሚያጋጥሙ እንረዳለን፡፡ ነገር ግን ችግሮችን ተናግሮ መፍትሔ ከማፈላለግ ይልቅ መደበቅ እየበዛ ነው፡፡ ከአቅም በላይ የሆኑ ችግሮች ሲፈጠሩ ሕዝብን ይቅርታ ጠይቆ በትዕግሥት እንዲጠባበቅ ከማሳወቅ ይልቅ ለአላስፈላጊ መላምቶችና ውዥንብሮች መዳረግ እየበዛ ነው፡፡ ችግሮችን ቢቻል በግንባር ካልሆነም በሚዲያ ቀርበው ማስረዳት የሚጠበቅባቸው ሹማምንት መደበቅን የተለመደ ተግባር በማድረጋቸው፣ ማብራሪያና ይቅርታ የደረሱበት ጠፍቷል፡፡
ሕዝቡ በውኃ እጦት ምክንያት ምግቡን ማብሰል፣ ንፅህናውን መጠበቅ፣ ሕፃናት ልጆችን መንከባከብ፣ ሕሙማንን ማስታመም፣ ወዘተ ሲያቅተው በግልጽ እየታየ ነው፡፡ አረጋውያንና ሕፃናት ሳይቀሩ ውኃ ፍለጋ ባልዲና ጀሪካን ተሸክመው በሌለ ጉልበታቸው ሲባዝኑ በአደባባይ ይታያል፡፡ ችግሩ እንዲህ ገዝፎ እንዴት ማብራሪያ መስጠት ይቸግራል? ይቅርታ ማለትስ ማንን ገደለ? የችግሩን መጠን በግልጽ አሳይቶ ሕዝቡን የመፍትሔ አካል ለማድረግ ለምን አልተፈለገም? ሌላው ቀርቶ ችግሮቹ እስኪቀረፉ ድረስ መንግሥት ራሱ ሕዝቡ እንዲታገስ ለምን ጥሪ አያቀርብም?
የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ከአንድ ግለሰብ እስከ ትላልቅ የግልና የመንግሥት ማምረቻ ተቋማት ድረስ እየፈጠረ ያለውን አበሳ እያየን ነው፡፡ በቀን ለበርካታ ጊዜያት ብልጭ ድርግም እያለ የተለያዩ ማሽኖችን፣ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን፣ ፍሪጆችን፣ ቴሌቪዥኖችን፣ የሲዲ ማጫዎቻዎችን፣ የማብሰያና መሰል ዕቃዎችን እያቃጠለ የዜጎችን ንብረት በማውደም ለከፍተኛ ኪሳራ ሲዳርግ ምንም እንዳልተፈጠረ ዝም ይባላል፡፡ በኃይል መቋረጥ ምክንያት ምርት ሲቆምና ዜጎች ማግኘት የሚገባቸውን ክፍያ ወይም ጥቅም ሲያጡም እንዲሁ ዝም ነው፡፡ ማብራሪያ ወይም ይቅርታ የለም፡፡
አገሪቱ የአፍሪካ ኅብረት መቀመጫና የትላልቅ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች መናኸሪያ ናት፡፡ በዚህም ምክንያት በተለይ በአዲስ አበባ በርካታ ኮንፈረንሶች ይካሄዳሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ‹‹ኮንፈረንስ ቱሪዝም›› በመባል በሚታወቀው ዘርፍ ስብሰባዎች በዓይነትም በመጠንም ጨምረዋል፡፡ በርካታ እንግዶች ከውጭ እየመጡ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ተስፋ ሰጪ ነገር ባለበት አገር ውስጥ የሞባይል ኔትወርክ ጥራት አደገኛ ችግር ውስጥ ገብቷል፡፡ በሞባይል ስልክ መነጋገር የማይቻልበት ደረጃ ላይ ነው ያለነው፡፡ የኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ከዔሊ ጉዞ ጋር ሲነፃፀር ቀርፋፋ ነው፡፡ ፋይበር ተበጠሰ በሚል ምክንያት አገልግሎት የሚቆምበት ጊዜ አለ፡፡ ኑሮዋቸውን በዚህ በዚህ አገልግሎት ላይ የመሠረቱ ዜጎች እየተጎዱ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የአገሪቱ የቴሌኮም አገልግሎት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ይህ ሁሉ ችግር እየታየ ግን የሚሰጠው ምክንያት ውኃ አይቋጥርም፡፡ ከዚህም ባለፈ በተገቢው መጠን ማብራሪያ ሲሰጥ አይታይም፡፡ ይቅርታ የሚለው ቃል ፈጽሞ ተዘንግቷል፡፡
ጠዋትና ማታ መንገድ ላይ ተኮልኩሎ በትራንስፖርት እጦት ለሚሰቃይ ሕዝብ ቀረብ ብሎ ለችግሩ መፍትሔ መፈለግ ይቅርና ችግሩ እንዴት እንደሚቃለል ማብራሪያ ተሰምቶ አይታወቅም ማለት ይቀላል፡፡ ጠዋት በሙሉ ኃይሉ በሥራ ገበታው ላይ ተገኝቶ አስተዋጽኦ የሚጠበቅበት ዜጋ በሠልፍ ምክንያት ተንገላቶ ሥራው ላይ አርፍዶ ሲገኝ ምን ዓይነት ውጤት ይጠበቅበታል? ከቀን የሥራ ድካም በኋላ ወዲያውኑ ትራንስፖርት አግኝቶ ለነገ ለመዘጋጀት ቤቱ በጊዜ መድረስ ያለበት ዜጋ ተመልሶ እዚያው ሠልፍ ጥበቃ ሲገባ፣ ችግሩን ተገንዝቦ መፍትሔ ማፈላለግ ያለበት አካል ሳይገኝ ሲቀር ምን ይባላል? የትራንስፖርት ዕጦት ችግሩ የተሽከርካሪዎች አቅም ማነስ? የቀጣና ሥምሪት አለመጣጣም? ወይስ ሌላ ተብሎ ይጠናል? ሰምተን አናውቅም፡፡ ማብራሪያና ይቅርታ ብርቅ ሆኗል፡፡
በተለያዩ የመንግሥት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ያለው አሠራር ደካማነትና የአገልግሎት ፈላጊዎችን ፍላጎት ያላማከለ መሆኑ የችግሩን ፅናት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡ ‹‹ደንበኛ ንጉሥ›› ነው የሚለው የቢዝነሱ ዓለም ቋንቋ ተረስቶ ‹‹ደንበኛ ጥገኛ›› ነው የተባለ ይመስላል፡፡ የመንግሥት አገልግሎት መስጫ ተቋማት ሕዝቡን የሚያስተናግዱበት የሥነ ምግባር መመርያዎች ተብለው የተዘረዘሩ ጽሑፎችን ለሚመለከት ሰው ቀልድ የተያዘ ነው የሚመስለው፡፡ ‹‹የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን ራዕይ እናሳካለን›› የሚል መፈክር ከራስጌው የሰቀለ ሹም አገልግሎት አሰጣጡን ማቀላጠፍ ተስኖት ሲያንቀላፋ ሲታይ ያሳፍራል፡፡ የራሱን ሥራ በአግባቡ መሥራት ያቃተው ሰው የሌላ ሰው ራዕይ አሳካለሁ ብሎ ሲመፃደቅ ማየት በራሱ አሳዛኝ ነው፡፡
በሕዝቡ ከፍተኛ ስሞታ እየተነሳባቸው ያሉ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ማብራሪያ መስጠትም ሆነ ይቅርታ መጠየቅ ነውር ሆኖባቸዋል፡፡ ስለዚህ እንዲህ ዓይነት አስመራሪ ሁኔታ በሕዝቡ ውስጥ ሲያጋጥም፣ መንግሥት ተነሳሽነቱን ወስዶ ችግሩን በመመርመር አስቸኳይ ዕርምጃ መውሰድ አለበት፡፡ ተገፋፍቶ ሳይሆን በገዛ ፈቃዱ ችግሩን አጣርቶ ለሕዝቡ ማስረዳት ጊዜ የማይሰጠው ተግባሩ ሊሆን ይገባል፡፡ በየተቋማቱ ብልጭ ድርግም እያሉ የሚደረደሩ የፌዝ ምክንያቶች ይቁሙ፡፡ በሕዝብ ላይ እያፌዙ ያሉ ሹማምንት በቃችሁ ይባሉ፡፡ በሐሰተኛ ሪፖርቶች የሚያጭበረብሩ ገለል ይደረጉ፡፡ ይብቃቸው፡፡
በሕዝብ ላይ እየተፈጸሙ ያሉ አሻጥሮችን ተከታትሎ የማስቆም ኃላፊነት ያለበት የመንግሥት ትልቁ አስፈጻሚው አካል ነው፡፡ ቢሮክራሲው በሙስና ተተብትቦ መሥራት እየተሳነው ነው፡፡ በአቅም ማነስ ምክንያት ሥራዎች እየቆሙ ናቸው፡፡ መንግሥት በቢሮክራሲው ውስጥ ያለውን የተሸፋፈነ ችግር መርምሮ ለሕዝቡ በግልጽ ማስረዳት አለበት፡፡ ሕዝብ የማወቅ መብት አለው፡፡ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ለተፈጠሩ ችግሮች መንግሥት በአደባባይ ሕዝቡን ይቅርታ ይጠይቅ፡፡ ይቅርታ መጠየቅ ከበሬታ ያስገኛል እንጂ አያዋርድም፡፡ የመልካም አስተዳደር ችግር ከላይ እስከ ታች መንሰራፋቱን መንግሥት በማያወላዳ ሁኔታ ማመን አለበት፡፡ ከመወሰን ይልቅ ውሳኔ ማዘግየት፣ ከመፈጸም ይልቅ በይደር ማቆየት፣ ችግሩን በግልጽ ከማስረዳት ይልቅ ማድበስበስ፣ ለመፍትሔ ከመንቀሳቀስ ይልቅ ዳተኝነት በዝቷል፡፡ ማብራሪያና ይቅርታ ተዘንግተው ግልጽነትና ኃላፊነት ተረስተዋል፡፡ በየቦታው መደበቅ በዝቷል፡፡ በመሆኑም መንግሥት መደበቁን አቁሞ ለሕዝብ ትክክለኛውን መረጃ ይስጥ! መደበቅ ይብቃ! ምንጭ ሪፖርተር ( ር ዕሰ አንቀጽ )
No comments:
Post a Comment